እሰይ ሰማይ ጠራ
ምድሯ ልታፈራ
ዕፅዋት ሊያብቡ
እንሥሣት ሊጠግቡ
ጉሙም ጠርጎ ሄደ ጭጋጉም ገፈፈ
አዲስ ዘመን መጣ ግዜውም ከነፈ
ደህና ሁን ነጎድጓድ አንተ ዋልክና ደፍ
በቅርብ ላንገናኝ ቃላችንን ላናጥፍ
ብርሃን ተገለጠ
የዘመናት ቅምር በስንዝር በለጠ
አዲስ ሥራ እንጀምር ዘመን ተለወጠ
ደመናው ተነነ
ጢሱ ተበተነ
የፀሐይም ብርሃን ሙቀቱ ገነነ
ትናንትም አርጅቶ ስሙም አምና ሆነ
የእንቁጣጣሽ ትዝታ
ትዝ አለኝ
እንኳን ተዘዋወርክ ወደ አዲሱ ዓመት
እንኳን አደረሰህ ለዐውደ ዓመት እለት
የማውቃቸው ሲሉኝ ከልብ በመመኘት
ትዝ አለኝ ትዝ አለኝ
መልካም እንቁጣጣሽ መልካም አዲስ ዘመን
እንኳን አብረን ደረስን
ይድገመን በብዙ ደጋግሞ ይድገመን
በኛ በሁላችን ትደግ ሀገራችን
ብለው ሲናገሩ የመንደሩ ልጆች
ወጣቶች ገና ቡቃያዎች
ትዝ አለኝ
በሣህን ዳቦው ሲደረደር
በዋንጫ ጠላው ሲንቆረቆር
አዮሃ አበባዬ
ሲሉ ወንዶቹ
አደይ የብር ሙዳይ
ኮለል በይ ሲሉ ሴቶቹ
እደጉ ብለው ሲመርቋቸው
ሽማግሎቹ
ታወሰኝ ትዝ አለኝ
የእንቁላል ልጆች የእንቁላል እናቶች
ፈርተው ተደናግጠው
ሲጮሁ ሲያለቅሱ ማሩን ተውን ብለው
ተቀልተው ሲበሉ ተቆርጦ አንገታቸው
የቅርጫት ሥጋ አንሱ ልጅ መሳይ ላኩና
ሥጋው አንዳገር ነው ጮማም አለውና
የመንደሩ ሰዎች ጥሪያቸው ታወሰኝ ታየኝ አሁን
ገና
የእንግጫ ጉንጉን
ታስሮ በራሳችን
ምኞት ተመኝተን
ዓውደ ዓመት ሌላ ዓመት ይደጋግመን ብለን
ታወሰኝ
’’እማማ እንዳለች አንድ ግዜ ኑና
እንጠጣ እባካችሁ አንድ ስኒ ቡና’’
እያለ ሲለፍፍ በረፋድ ተነስቶ
አፉ በጣም ወዝቶ ጉንጩ እጅግ ፋፍቶ
ሆዱ ሞላ ብሎ ወደፊት ተገፍቶ
ዳቦ መሳይ ጎርሶ
አዲስ ሱሬ ለብሶ
ሞንደል ሞንደል ሲል ከቤታችን መጥቶ
የማሚቱ እናት ልጅ የአዲሱ ዘመን ሰው ታየኝ
በመንፈስ በሩን አልፎ ገብቶ
ታየኝ ታወሰኝ
አበባ እንቁጣጣሽ ልጆቹ ሲያመጡ
ገብተው ከመንደሩ ለሰዎች ሲሰጡ
ሲሳሳቁ ከውጭ እየተሯሯጡ
ታወሰኝ
ትናትም ቀን ነበር እንደዛሬ ሁሉ ከሌለት በፊት
ዛሬም በበኩሉ ከሌሊት በኋላ ይሆናል ትናንት
የግዜ አቀማመር
የዕድሜ አቆጣጠር
የዘመን ህላዌ የሠአቱ ምስጢር
ይገለጥ ይፈታ ይበጠር ይንጠርጠር
ትናንትና ዛሬ ነገ ሲባል ውሎ ለትናንቱ ነገ
የነገውን ዛሬ ትናንት ማድረግ ከፈለገ
ዘመን ተለወጠ ብለህ የምትጮኸው
ተጠየቅ በናትህ ተጠየቅ ባባትህ
አምና እንደምን ነበርክ ዘንድሮስ እንዴት ነህ?
ያኔ በዛሬው ቀን ምን ምን ታውቅ ነበርህ
የርቀትህ መጠን የሀሳብህ ስፋት
የነገርህ ወሰን እውቀትና ርዝመት
ከየት ተጀምሮ በየት በየት አልፎ እምን ላይ
ያበቃል
የትኛውን ጨርፎ የቱን አጠቃሎ ከየትኛው አርፎ
ምን ይመለምላል
ሃሳበ ግትር ነህ ዛሬም እንደወትሮ
ማን አለብኝ የሚል ሞኛ ሞኝ ደንቆሮ
እንግዲህ ወዳጄ ዘመን ቢለወጥም
መስከረም ቢጠባም
መንፈስህ ታድሶ ካልተለወጠ አብሮ
ከአምናው ከአቻምናው
ከትናንት በሽታህ አልዳንክም ዘንድሮ
ከቀድሞው ሥርአተ ትምህርት የ9 ክፍል የአማርኛ
መማሪያ መጽሐፍ ላይ የተወሰደ
ለማከብራችሁ ወዳጆቼ በሙሉ ይልቁንም በዚህ ስርዓተ
ትምህርት በዚህ ክፍል አብራችሁን ለነበራችሁ ወንድሞቼና እህቶቼ እንዲሁም ይህችን ግጥም ለፈተና ተማሪ ፊት ላነበባችኋት በሙሉ መልካም
ትዝታ ይሁንላችሁ
መልካም አዲስ ዓመት
ዘመኑን የማስተዋል ዘመን ያድርግልን
መ/ር ሰሎሞን ፋንቱ 2007 ዓ.ም
No comments:
Post a Comment